Thursday, January 23, 2014

አምባገነናዊ ሥርዓት “ህጋዊ” የሆነባት ሀገር - “ኢትዮጲያ”
=====================================
በናትናኤል ካብቲመር ኦስሎ ኖርዌይ January 21, 2014

አምባገነናዊ ስርዓት መሰረታዊነት በጎደለው ንድፈ ሃሳብ ላይ የተመረኮዘ የሃገርንና የህዝብን ችግሮች ከመፍታት ይልቅ የስርዓቱን እድሜ ለማራዘም ሆን ተብሎ በተቀረፁ ፖሊሲዎች የታጀለ ፣ የጥቂቶችን ብቻ መብትና ጥቅም የሚያስከብር አፋኝ ስርዓት ነው። በአንፃሩ ደግሞ ዲሞክራሲያዊ ስርዓት የአንድን ማህበረሰብ ፖለቲካዊ ፣ ኢኮኖሚያዊ እና ማህበራዊ ችግሮችን በዘላቂነት በመፍታት ፣ የሁሉን ዜጋ መብት አክብሮ በማስከበር እንዲሁም በእኩል አይን በማየት ፣ የተለያዩ ሁለንተናዊ የዘላቂ እድገት አማራጮችን ለብዙሃኑ በሚጠቅም መልኩ ሥራ ላይ በማዋል የሚል መሰረታዊ ንድፈ ሃሳብ ላይ የሚመሰረት ፣ የሃገርን እድገትና ልማት ለዘለቄታው አረጋግጦ ለዜጎችም የተሻለ የኑሮ እድል የሚፈጥር ስርዓት ነው።

በአለማችን በተለያዩ ሃገራት ያሉ አምባገነናዊ መንግስታት ፖለቲካዊ አወቃቀራቸውን ዲሞክራሲያዊ ለማስመሰልና ህዝባቸውንም ሆነ ሌሎች መንግስታትን ስለስርዓታቸው ዲሞክራሲያዊነት ለማሳመን ሲጥሩ የወያኔ መንግስት ግን አምባገነናዊ ስርዓት በህዝብም ሆነ በተለያዩ መንግስታት ህጋዊ ተቀባይነት እንዲያገኝ በድፍረት ሲደክም ይታያል። ላይ ላዩን ዋናው ጠላታችን ድህነት ነው እያለ አምባገነናዊ ከሆነ የፖለቲካ ስርዓት የመነጨውን ለወያኔ ካምፓኒዎች ብቻ ተመቻችቶ የተቀመረ የተሳሳተ ኢኮኖሚያዊ አወቃቀር በማራመድ የኑሮ ውድነቱን በማናር ከዛሬዎቹ በተጨማሪ የነገዎቹን ብዙ ድሀዎች በመፍጠር ላይ ይገኛል።

የወያኔ መንግስት አፈቀላጤዎች እየተቀባበሉ እንደሚወተውቱት ለህዝቡ ከዲሞክራሲ ይልቅ ሰላም የሚሉት ዘይቤ ተጨባጭነቱ አጠያያቂ መሆኑ ግልፅ ነው። ምክንያቱም የዜጎችን መብት በመርገጥ እና በጉልበት የመብት ጥያቄዎችን በማፈን የሚመጣ የይስሙላ ሰላም ዘላቂና አስተማማኝ አለመሆኑ ብቻ ሳይሆን ውስጥ ውስጡን የበረከተ ጥላቻ ፣ ቅሬታና ቂም በመፍጠር ለመጪው የሀገር ሰላምና አንድነት መሰረተ ሰፊ ስጋት መሆኑ አሌ የማይባል ሐቅ ነው።
የወያኔ መንግስት ከጫካ ጀምሮ ወጥ የሆነ ፖለቲካዊ ስርዓትን ለመገንባት ከመሞከር ይልቅ በተለያዩ ጊዜያት የተለያዩ ሀገራትን የፖለቲካ ስርዓት እያጣቀሰ አንዴ እንደዚህኛው ሀገር ሌላ ግዜ ደግሞ እንደዛኛው ሀገር አይንት ስርዓት እንገነባለን እያለ እድሜውን ሲያራዝም ቆይቷል። በስልጣን ቆይታውም ስርዓቱ የፈጠራቸውንና የሚፈጥራቸውን ኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ ችግሮችን በግልፅነት ለይቶ ከማውጣትና በተገቢው መንገድ ከመፍታት ይልቅ በማድበስበስና በማቃለል ባገኘው አጋጣሚ ሁሉ የስርዓቱን መልካምነት በመስበክ አምባገነናዊነቱን ተቀባይነት እንዲያገኝ ሲጥር ይስተዋላል።

ምዕራባዊያንም ሆኑ ሌሎች በርካታ ዲሞክራሲያዊ ስርዓት የሰፈነባቸው የአለማችን ሀገራትን እንደምሳሌ ወስደን ለምን አምባገነናዊ ስርዓትን አስወግደው ዲሞክራሲያዊ ስርዓትን ለመግንባት ለዘመናት ታገሉ? የሚል ጥያቄ ብናነሳ መልሱ ቀላል ነው። ለአንድ ሀጋር ዘላቂነት ያለው ሁለንተናዊ እድገትና ልማት ለማምጣት የዲሞክራሲያዊ ስርዓት ግንባታ ብቸኛው አማራጭ ስለሆነ ነው። በሀገራችንም ያለውንም ሞልቶ የፈሰሰ ዘርፈ ብዙ ችግር ለመቅረፍም ይህንኑ አማራጭ መከተል ብቸኛ መፍትሄ መሆኑ አጠያያቂ አይደለም።

በሀገር ውስጥም ሆነ ከሀገር ውጪ የሚንቀሳቀሱ የፖለቲካ ፓርቲዎችም ሆኑ ማህበራት ምንም እንኳን ዝርዝር የፖሊሲ ቀረፃና የትግል አቅጣጫቸው ለየቅል ቢሆንም የዲሞክራሲያዊ ስርዓት ግንባታ የኢትዮጲያን ስር የሰደደ ችግር መፍትሄነቱን ጥያቄ ውስጥ የሚከት የለም። ይህንንም ስርዓት ተመራጭ ያደረገው ነባራዊዎቹን ኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ ችግሮችን ከመፍታቱም ባሻገር ዳግም እንዳይፈጠሩ መከላከሉ ፣ የሰው ልጆችን ሁሉ እኩል አድርጎ ማየትና መብታቸውንም በእኩልነት ማክበር እንደመሰረታዊ መርህ መከተሉ ነው።

በአሁኑ ግዜ የሰው ልጆችን የሚያበላልጡና እኩልነቱን ጥያቄ ውስጥ የሚያስገቡ ለምሳሌ እንደዘውዳዊ አገዛዝ ዘመን በእግዚአብሔር ለገዢነት የተመረጠ ዘር ብሎ መለየት እንዲሁም እንደ ባሪያ ፍንገላ ዘመን ነጭ ከጥቁር የሚሻል ነው ማለትና የመሳሰሉት ነገሮች ከህጋዊነት ውጪ ሆነዋል። ነገር ግን በሀገራችን ኢትዮጲያ ቅርፁን በለወጠ መልኩ የሰው ልጆችን መሰረታዊ የእኩልነት መርህ የሚጥስ የስልጣንና የጥቅም አድሎ “ያለፈውን ስርዓትለመጣል ስለታገሉ” ወይም “የምንትስ ዘር ስለሆኑ” ተብሎ የህዝብ አገልጋይነት ላይ ማተኮር የሚገባውን የመንግስት ስልጣን እንደ ውለታ መመለሻና ኩርፊያ ማባበያ በስጦታ መልክ የማበርከት በግልፅ የሚነገርና የሚታይ ፀረ ዲሞክራሲያዊ ኩነት በመከላከያና በተለያዩ የመንግስት አካላት ተንሰራፍቶ ይታያል።

በጥቅሉ የዲሞክራሲያዊ ስርዓት ግንባታ ተግባራዊነቱ የሚጀምረው “በብዙሃኑ” (majority) የተወደደውንና የተመረጠውን የፖለቲካና ኢኮኖሚ አመለካከት የስልጣን ባለቤት በማድረግ ፣ “በብዙሃኑ” (majority) እና “በአናሳው” (minority) መካከል ህጋዊነት የተላበሰ የተቻቻለ የአገዛዝ ስርዓት በመፍጠር ፣ “ብዙሃኑ” ና “አናሳው” የሚባሉትን ወገኖች በፖለቲካዊና ኢኮኖሚያዊ አማራጭ አመለካከታቸው ብቻ በመለየት ነው።

የሀገራችን አምባገነን መንግስት ግን “ብዙሃኑ” ና “አናሳው” የሚባሉትን ወገኖች ከፖለቲካዊና ኢኮኖሚያዊ አማራጭ አመለካከታቸው ይልቅ ከዘርና ብሔር ጋር አቆራኝቶ የስርዓቱን ዲሞክራሲያዊነት ይሰብካል። ክቡር የሆነውንና የማንነት አይነተኛ መገለጫ የሆነውን ብሔር ባልተገባ መልኩ የጊዜያዊ ፖለቲካዊ ጥቅምን ከማስከበር አንፃር ሲመነዝረው ይስተዋላል። ብሔር መሰረታዊ ከሆኑት የማንነት መገለጫዎች የተከበረውና ዋነኛው መሆኑ አጠያያቂ ባይሆንም ከፖለቲካና ዲሞክራሲያዊ ስርዓት ግንባታ ጋር የሚኖረው ቁርኝት በጥንቃቄና ግልፅ በሆነ መልኩ ሀገርን በዘላቂነት ከሚጠቅምና የዜጎችን ተጠቃሚነት ከሚያረጋግጥ አማራጭ የፖለቲካ ንድፈ ሀሳብ ሳይዋቀር እንደ ህወሃት ዛሬን ለማለፍ እንደነገሩ ለየብሄሩ ተሰርቶ ከተለጠፈ ወደፊት ከሚፈጥረው አስከፊ አደጋ ባሻገር ሀገራዊ ስሜትን በዘላቂነት ያኮስሳል።
የወያኔ መንግስት ከማንኛውም መንግስት እንደሚጠበቀው ለዜጎች ህልውናና ደህንነት አፅንኦት በመስጠት ምሳሌ በመሆን ለህግና መሰረታዊ መብቶች የዳበረ ክብር ያለው ፣ ለሀገሩ ስር የሰደደ ጥልቅ ፍቅር ያለው ማህበረሰብ ከመፍጠር ይልቅ አምባገነናዊ ስር አቱን በይስሙላ ህግጋት ለመደገፍ እንደ ፀረ ሽብር አይነት ህጎችን ለጊዜያዊ የስልጣን ጥቅም ሲባል በማጣመም ስርዓቱን የተቃወሙትን ሁሉ እንደወንጀለኛ በመፈረጅ ማሰሩን አማራጭ ሃሳቦችን በግልፅ ማፈኑን ስራዬ ብሎ ተያይዞታል። ለስልጣን ጥምና ቆይታ ካፀደቃቸው የተሳሳቱ ፖሊሲዎች የተለዩ ምክንያታዊነት ያላቸው አማራጭ ሀሳቦችን የሚያመነጩ አካላትን እንደ ሀገርና ህዝብ ባላንጣ በመፈረጅ የሰከነ ውይይት ከማድረግ ይልቅ ለዲሞክራሲያዊ ስርዓት ግንባታ እንደመሰረት ድንጋይ የሚያገለግሉ የተለያዩ የፖለቲካና የሲቪክ ማህበራትን እንዲሁም የተለያዩ የነፃ ሚዲያ ተቋማትን በማፈራረስና ከሃገር በማባረር የተቀሩትንም ወደ ስርዓቱ መጠቀሚያነት በግድም ሆነ በማባበል በመለወጥ ስልጣን የህዝብ የሚሆንበትን ቀን እያራቀ ይገኛል።የድርጊቱን ፀረ ዲሞክራሲያዊነት እንዲሁም የህጉን የአተረጓጎም መጣመምና መፋለስ ጥያቄ ሲነሳ የህጉን ከሌሎች ሀገራት ህግጋት ጋር ያለውን ተመሳሳይነት ብቻ በመደጋገም ዋና ጥያቄ የሆነውን የህጉን የአተረጓጎም ጥመት አድበስብሶ ያልፋል።

ከቅርብ ጊዜያት ወዲህም የዚህ አፋኝ ስርዓት ቀጥተኛ ተጠቃሚና አቀንቃኞች በተለያዩ የማህበራዊ ሚዲያዎች መንግስታቸውን በማሞካሸት አምባገነናዊ ስርዓቱ ህጋዊ ተቀባይነት እንዲያገኝ ሲሰብኩ ማየት የተለመደ ሆኗል። ዘላቂ የሆነ የዲሞክራሲና የኢኮኖሚ እድገት የሚያረጋግጡ አማራጭ ሀሳቦች የሚያቀርቡ አካላትን በአደባባይ እየዘለፉ በግልፅ የሚታየውን የመብት ረገጣና ከመጠን ያለፈ የኑሮ ውድነት ችላ በማለት ስለመንግስታቸውን ቅዱስነት አይናቸውን በጨው አጥበው ይሟገታሉ። አማራጭ የፖለቲካ አስተሳሰብ አቅራቢ አካላትን በፅንፈኝነት በመፈረጅ ጥቃቅን ችግሮቻቸውን በማግዘፍ የወያኔ መንግስትን ፍፁም ዲሞክራሲያዊነት ለማሳመን ይታትራሉ። “ሌሎች ሃገራት እንደምሳሌ የሚጠቀሙበት መንግስት አለን” ብለው በድፍረት ይናገራሉ። በተለያዩ የምዕራባዊ ሃገራት የሚኖሩ የወያኔ ደጋፊና አባላት በሚኖሩበት ሀገር ያለውን የጎለበተ የዲሞክራሲ ስርዓት የፈጠረውን የህግ የበላይነትና የዜጎች መብት መከበር በጎ ገፅታ እያዩ እንኳን አቋማቸውን ማስተካከልና ያንኑ ለሃገራቸው መመኘት ሲገባቸው የኑሮ ውድነት ያጎበጠው የሃገራችን ህዝብ ጫንቃ ላይ የተጫነው አምባገነናዊ ስርዓት “ፍፁም” የሆን መልካምነት ሽንጣቸውን ገትረው ይሟገታሉ። በተወሰነ መልኩ እንኳን በጎ የሚባሉትን የፖለቲካና ኢኮኖሚ ገፅታዎች በሃገራችን ይፈጠር ዘንድ እንደ አስተያየት ከመጠቆም ይልቅ አምባገነናዊ ስርዓቱን የማይሳሳት ፣ ሁሉን ያሟላና ቀጥተኛ ብለው አፋቸውን ሞልተው ይናገራሉ።

የዲሞክራሲያዊ ስርዓት ግንባታ መጀመር ሀገራችንን ለዘመናት ከተቆራኛት የችግር ደዌ ከማላቀቅ አልፎ ዘላቂ የሆነ መሰረታዊ መብቶች መከበርና ለህግ የበላይነት መስፈን ይረዳል። የኢትዮጲያ ህዝብም ይህንን በሚገባ ያምናል ፣ ያውቃል ፣ የስርዓቱንም አስፈላጊነት በምርጫ 97 ወቅት አደባባይ ወጥቶ ጠይቋል። ያሉበትንም ዘርፈብዙ ችግሮች በአስተማማኝ መልኩ ለመፍታት አምባገነናዊ ስርዓትን በማስወገድ ዲሞክራሲያዊ ስርዓትን በመገንባት መሆኑን አውቆ ተረድቷል። ነገር ግን የወያኔ መንግስት የዲሞክራሲያዊ ስርዓት በመገንባት ሂደት ውስጥ መሰረታዊ ሚና የሚኖራቸውን ህዝባዊ አንድነት ኃይልና መሰረቱ የጠነከረ የትብብር ፖለቲካ እንዲዳከምና ዳግም እንዳይፈጠር ሌት ተቀን በማሴር ፣ ተሳታፊዎቹንም በማሰርና ከሀገር በማባረር በጉልበተኝነት የህዝብን ድምፅ አፍኖ አስቀረ። ብሎም መሰረታዊ ፣ ሰብዓዊና ዲሞክራሲያዊ መብትን አክብረው የሚያስከብሩና እውነተኛ የሆነ ሁለንተናዊ የሀገር እድገት ለማረጋገጥ ተግተው የሚሰሩ የዲሞክራሲ አርበኞችን ከመፍጠር ይልቅ የህዝባቸው ችግርና መብት መረገጥ የማይጎረብጣቸው አምባገነናዊውን ስርዓት አምላኪ ወገንተኛ ግለሰቦችን እንደ ህዝብ ተወካይ በመመልመል በ 2002 ምርጫ 99.6 በመቶ አሸነፍኩ ብሎ በሚያሳፍር ድፍረት ተናገረ።

ይዘገይ ይሆን ይሆናል እንጂ በህዝብ ፈቃድና ይሁንታ ተመርጦ የህዝብ አገልጋይ የሚሆን ዲሞክራሲያዊ መንግስት የመፈጠር አይቀሬነት ሁላችንም እናውቃለን። የህግ የበላይነት ፣ የግለሰብም ሆነ የብሄር መብት እንዲሁም ክብር ፣ ዘላቂነት ያለው ሁለንተናዊ የኢኮኖሚ እድገት የሚረጋገጠው አምባገነናዊውን ስርዓት ተወsግዶ ዲሞክራሲያዊ ስርዓት ሲገነባ መሆኑንም እናምናለን። ይህም እውን ይሆን ዘንድ ጠንክረን እንታገላልን።
በአምባገነኖች ውድቀት ላይ ዲሞክራሲያዊነት ይለመልማል !!

No comments:

Post a Comment